ልዩ ምግብ

Life, Health, Religion, Social, General Question
Forum rules
No cursing, bad language and offend other users !
No pornographic images or links!
This forum monitored regularly. We will BAN users without warning for not obeying rules.
እባክዎ የፎረሙን ህጎች ያክብሩ::
selam sew
Leader
Leader
Posts: 692
Joined: 08 Feb 2011 11:14
Contact:

ልዩ ምግብ

Unread post by selam sew »

💫ልዩ ምግብ!

☀️አንድ ሰው፣ በአንድ ከሰዐት፣ ወደ አንድ ሆቴል ያቀናል። በጥንቃቄ የምግብ ዝርዝሩን ካነበበ በኋላ የሚፈልገውን መርጦ ያዛል። ከ20 ደቂቃ በኋላም ወንዶችና ሴቶች በቡድን በመሆን ወደ ሆቴሉ ይገቡና በጋራ ምግብ ያዛሉ። ታዲያ ከእርሱ ትእዛዝ ቀድሞ የሰዎቹ ትእዛዝ ይደርስና ይስተናገዳሉ። እነርሱ ሲበሉና ከልባቸው እየሳቁ ሲጫወቱ በትዝብት ዓይን ይመለከት ጀመር። ይባስ ብሎ፣ ከመካከላቸው አንደኛው፦ "በሆቴል ውስጥ ያሉትን ሁሉ እንዴት እንደሚያውቃቸውና እንዴት ነገሮች ሁሉ ለእርሱ በፍጥነት እንደሚከናወኑለት" ጉራውን ሲነዛ ሰማው። ይህን ጊዜ እየተሳለቁበት እንደሆነ ተሰማውና ተነስቶ ሊሄድ አሰበ፣ ከዚህ በላይም መታገስ አይኖርብኝም በማለት አስተናጋጁን ይጠራል።

☀️አስተናጋጁ ግን ትህትና በተሞላ ቃልና በሚማርክ ፈገግታ፦ "የእርሶ ልዩ ትእዛዝ በመሆኑ ዋናው ሼፍ ራሱ፣ ያዘዙትን ምግብ እያዘጋጀሎት ይገኛል። የእነርሱ ትእዛዝ በፍጥነት የደረሰበት ምክንያት- ዋናው ሼፍ በእርሶ ትእዛዝ ባተሌ ስለሆነ በአባሪ ተማሪዎች የተሠራ በመሆኑ ነው። ለዚህ ነው የነርሱ ትእዛዝ ከርሶ ትእዛዝ ቀድሞ ሊደርስ የቻለው ጌታዬ፤ እባክዎን ትእዛዞ እስኪደርስ ድረስ ጭማቂ እየጠጡ ይጠብቁ" አለው።

☀️ይህን ጊዜ ተረጋግቶ መጠበቁን ያዘ። ከደቂቃዎች በኋላም፣ የናፈቀው ምግብ ደርሶ- 6 አስተናጋጆችም ቀርበው በጠረጴዛው ዙሪያ ያስተናግዱት ጀመር። አንድ በውል ያላወቀውም ፊት፣ የሆቴሉ ባለቤት (ኋላ ላይ፣ ከተለያዩ ብዙ ዓመት የሆነው፣ የልጅነት ጓደኛው መሆኑን ያወቀው ሰው) ይመጣል። ለካ ገና ወደ ሆቴሉ ሲገባ አስቀድሞ አይቶት ኖሮ፣ እርሱን ለማስደሰት ሲል ያዘዘውን ቀለል ያለ ምግብ በ *ልዩ ትእዛዝ* በራሱ እጅ ሲሠራለት ቆይቷል።

☀️ታዲያ ይህ ሁሉ ሲሆን በነገሩ ትኩረታቸው የተሳበው፣ በሌላኛው ጠረጴዛ ያሉት ተስተናጋጆች ዐይናቸውን መንቀል እስኪያቅታቸው ድረስ በአግራሞት ፈዘው ይቀራሉ። ወዲያውም "እኛስ ስለምን እንደርሱ ዐይነት መስተንግዶ አላገኘንም?" በሚል ማጉረምረም ጀመሩ።

☀️በህይወትም እንደዚህ ነው። አንዳንድ ሰዎች ካንተ ፈጥነው ተራምደዋል፣ ካንተ ቀድመው የሚፈልጉትን አግኝተዋል፤ አንተ ግን ወደ ኋላ እንደ ቀረህ ይሰማሃል፣ ሁሉም ነገር እንደጠበከው አልሆን ብሎህ ታክተሃል። እንደውም አንዳንዶቹ ካንተ በተሻለ እንዴት ሰዎችን እንደሚያውቁ፣ ካንተ ይልቅ እንዴት ብልጣብልጥ እንደሆኑ፣ እንዴት ከብዙዎች ጋር የቅርብ ግንኙነት እንዳላቸው፣ እንዴት ስኬታማ እንደሆኑ፣ በቀላሉ ሳይለፉ ገንዘብ እንዴት እንደሚያገኙ--በዚህ ሁሉም እንዴት በህይወታቸው ደስተኛ እንደሆኑ ሲናገሩ ትሰማለህ። ይባስ ብለው፣ አንዳንዶቹ ደግሞ ይስቁብህና ይሳለቁብህም ይሆናል።

☀️አንተም፤ "ለምን እንዲህ ሆነ?" ብለህ ከመጠየቅ ይልቅ፥ "ለምን የነርሱ እንዲህ ሊሆን ቻለ?፣ ለምን በነርሱ ተቀደምኩ?፣ ከነርሱ በምን አንሼ ነው?"...እያልክ ራስህን ከሰዎች ጋር በማነጻጸር ስሌት ውስጥ ዘወትር ተጠምደህ ይሆናል። ከነርሱ አንጻርም ያንተ ስኬት ስለዘገየ፣ ብዙ በመጠበቅ ደክመሃል። ሁሌም ቢሆን ትኩረትህ እነርሱ ላይ ስለሆነ ከነርሱ የምትሰማው ፌዝና ስላቁ ተደማምሮ- ኃፍረትና ውርደት ተሰምቶህ፣ ምናልባትም በህይወትህ እንኳን ተስፋ ቆርጠህ፣ ከፍተኛ ጭንቀትም ውስጥ ገብተህ ይሆናል።

አይዞህ! አትጨነቅ!

🎹ይሀውልህ፤ የህይወትህ ባለቤት የሆነው ፈጣሪህ- ገና በዕድሜህ ማለዳ አይቶህ፣ እንደሚስቁብህ ሰዎች ዐይነት ቀላል ምግብ/ስኬት ሊሰጥህ ስላልፈለገ ነው- ነገሩ የዘገየብህ። እንደ ሌሎቹ ብልጣብልጥ ባለመሆንህ፣ አቋራጭ መንገድ ባለመጠቀመህና ያለልፋት ነገሮችን ለማግኘት ባለመፈለግህ- ርቱእ የሆነውን ህይወት፣ በትእግስትም የሚገኘውን ስኬት ታጣጥመው ዘንድ በፈጣሪ የተሻለ ስለታሰበልህ ነው-- በቶሎ ያልሆነልህ።

📖ብዙ የጠበክ የመሰለህም ያንተ ልዩ የሆነ ምግብ/ስኬት ስለሆነ ነው። ልዩ ምግብ ለማዘጋጀት ደግሞ ጊዜ ይፈልጋል፤ ያም ምግብ በዋና ሼፍ/ፈጣሪህ የሚዘጋጅ ነው። ስለዚህ አትጨነቅ! ይልቅ በትእግስት ጠብቅ። ራስህንም ከሌሎች ጋር በማነጻጸር አትድከም፣ ያንተ ምግብ/ስኬት ሲደርስ የቀናህባቸው መልሰው ሊቀኑ፣ የሳቁብህም አፋቸውን ሊይዙ እንደሚችሉ አስብ።
Post Reply

Return to “Ethio General .... ኢትዮ ማህበረሰባዊ ርዕሶች”